ፈቲነ ብእር ማለት አባቶቻችን ቀድሞ እንደ አሁኑ ዘመን ሳይስለጥን ብራና ዳምጠው ራምመው ብእር ቀርጸው ብእሩም፣ ቀለሙም፣ ብራናውም ለጽሑፍ ዝግጁ መሆኑን ለማረጋገጥ ፈቲነ ብእር ብለው ይሞክራሉ፡፡ ከዚያም ብእሩም ቀለሙም ከብራናው ስምሙ ከሆነ መደበኛውን የጽሑፍ ሥራቸውን ይቀጥላሉ፡፡ እኔም ይህን ማለቴ ለመምህር ዲበኵሉ የመጀመሪያ ሥራቸው ስለ ሆነ ነው፡፡ ሁሉም ጸሐፊ ሁኖ አማረኛ ከአማረኛ እያቀማጠሉ አንባቢውን በሚያሰለችበት ዘመን እንዲህ ያለ ግሩም ድንቅ የሆነ መጽሐፍ ምሥጢርን ከምሥጢር አሰናስለው ስላበረከቱልን እናመስግናለን፡፡
በ፪ኛ ከአትሮንስ ሥር ቊጭ ብለው ምሥጢር ጠይቀው ተምረው አደላድለው ምሁራን ሲጽፉ አንባቢ ያልተሰሙና ያልታወቁ ዐሳቦች ልዩ ልዩ የረቀቀ ምሥጢር ታሪክ ባህል የበለጠ እንዲታወቅ እድል ይፈጥራል፡፡
በ፫ኛ በየጉባኤ ቤቱ ዕውቀትን ፍለጋ ለሚደክሙ የአብነት ደቀመዛሙርት መነቃቃትና መነሳሣት ይፈጥራል፡፡ ስለዚህም ጥበብንና ዕውቀትን የሚሻ ሁሉ ይህን መጽሐፍ እንዲያነብ እላለሁ ንሥአ ለዛቲ መጽሐፍ ወብልዓ፡፡
መ/ር ሐረገወይን
በባሕርዳር ሀ/ስ የደ/ፀባይ ቀ/ገብርኤል ገዳም የቅኔና የመጻሕፍት መምህር